ቅዱስ ሲኖዶሱ ከአጣብቂኝ የሚወጣው ወደ ሓዋሪያቱ ቀኖናና ቀዳሚያን አበው ውሳኔዎችን በማገናዘብ ተመልሶ ስሕተቶቹን ሲያርም፥ ኢቀኖናዊያን ሹመኞችን ሲሽር ብቻ ነው
በትግራይ ቤተክርስቲያን ዙሪያ አያገባህም አርፈህ ዝም በል የሚል አስተያየት ተሰጠኝ።
ይህ ቤተክርስቲያን አንዲት ናት የሚለውን የዶግማ ትምህርት የሚቃረን አባባል ነው። እንኳንስ ትግራይ ውስጥ ባለችዋ ቤተክርስቲያን ግብፅ፣ አርመን፣ ሶርያ፣ ህንድ፣ ኤርትራ ባለችዋ ቤተክርስቲያን እኩል ባለጉዳይ መሆኔን ማሳወቅ እፈልጋለሁ። ዘረኝነት በቤተክርስቲያን ውስጥ ቦታ የለውም። ቅዱስ ሲኖዶስም ራሱን ቢያጠራ ደስ ይለኛል። እኔን አትናገሩኝ እነ አባ ኢሳይያስን ብቻ ተናገሩልኝ አይባልም። ነውር ነው። ለሻረው ቀኖና ይቅርታ ይጠይቅ። ሲኖዶስ ራሱ ቀኖና ነው የሚሉ አንዳንድ የዋሃንን እየተመለከትኩ ነው።
መጽሐፈ ሲኖዶስን ከሆነ ጥሩ ብላችኋል። የአምስት ኪሎውን ስብስብ ከሆነ ግን ተሳስታችኋል። ሲኖዶስ ራሱ ቀኖና ነው የሚለው አባባል የፈለገውን ዓይነት ውሳኔ ቢወስን ቀኖና አድርገህ ተቀበል እንደማለት ነው። ለምሳሌ ባለፈው ንጹሕ ኦሮሞ ሹመናል ብሎናል ሲኖዶስ። ስለዚህ ሲኖዶስ ቀኖና ስለሆነ ንጹሕ ኦሮሞ (የሌላ ዘር ያልተቀላቀለበት) መሾምን እንደ ቀኖና እንቁጠረው ይሆን??
ባለፈው እነ አባ ሳዊሮስ የኦሮሞና የብሔርብሔረሰቦች ሲኖዶስ ብለው 26 ሰዎችን ሹመው ነበር። ከዚያ ቅዱስ ሲኖዶስ አወገዛቸው። እንደገና በዐቢይ አማካኝነት ተደራደሩ። ሐምሌ ፱ ቀን ቅዱስ ሲኖዶስ ንጹሕ ኦሮሞ ሹመንላችኋል እንኳን ደስ አላችሁ አለን። ከዚያ አሁን ደግሞ እነ አባ ኢሳይያስ መንበረ ሰላማ ብለው 6 ሰዎችን ሾሙ። ቅዱስ ሲኖዶስ ባለፈው እንዳደረገው ተደራድሮ ንጹሕ ትግሬዎችን (የሌላ ዘር ያልተቀላቀለባቸውን) ይሾምልን ይሆን ይሆንን??? አባ ሰረቀ ያለው ልክ ነው ማለት ነው?
ቅዱስ ሲኖዶስ የሾማቸው ንጹሕ ኦሮሞዎች ወደፊት እነርሱም የሚሾሙት ንጹሕ ኦሮሞ ነው የሚሆነው ወይስ እንዴት ነው? በእናቱ አማራ በአባቱ ኦሮሞ፣ በአባቱ ኦሮሞ በእናቱ ትግሬ የሆነ ሰውስ አይሾሙም ማለት ነው?! ትላንትና የሆነ ትግሬ መነኩሴ አቡነ ተክለሃይማኖትን አማራ ናቸው ብሎ ሲያብጠለጥላቸው ሰማሁ። ብዙ አልገረመኝም። ወደፊት ንጹሕ አማራ ናቸው ተብለው የሚታሰቡ ቅዱሳንን የመጥላት ዘመቻ ይሠራል። ይኽው ትላንት ተጀመረ። በእርግጥ ቅዱስ ሲኖዶስምኮ ሲሾም ባለፈው ንጹሕ ኦሮሞ ብሎ ነው የሾመው። ጉዳዩ የሃይማኖት አይደለም። ጉዳዩ የዘረኝነት ነው። ዘረኝነትን ደግሞ ቤተክርስቲያን ትጸየፋለች። ቅዱስ ሲኖዶስ ብቃትን መሠረት ያደረገ ሰው ቢሾም መልካም ነበር። ችግር ችግርን እየወለደ ይኽው እስካሁን አለን። ውሸትን በሌላ ውሸት ማሸነፍ አይቻልም። ውሸትን ማሸነፍ የሚቻለው በእውነት ነው።
መውጫ:- ቅዱስ ሲኖዶስም፣ መንበረ ሰላማ ነን ባዮችም ሁላችሁም ይመራናል የምትሉትን እግዚአብሔር መንፈስቅዱስ ብታከብሩ መፍትሔው ቀላል ነው። እግዚአብሔር መንፈስቅዱስ በቅዱሳን ሊቃውንት አድሮ በቅዱሳት መጻሕፍት ምን አለን የሚለውን አይታችሁ እንድትወስኑ ነው። ቅዱስ ሲኖዶስ ባለፈው ቀኖና ሽሮ በዘር የሾማቸውን ስለእግዚአብሔር ብሎ ሹመታቸውን ቢተወው፣ "መንበረ ሰላማ" ነን ብለው በራሳቸው ጉልበት አጰጵሰናል የሚሉትም ከእልህ ወጥተው ክርስቶስን ቢፈሩና ስለክርስቶስ ብለው ሕገወጥነታቸውን ቢተውት መልካም ነው። ብልጽግናንና ሕወሀትን ፈርታችሁ ከምትወስኑ መንፈስ ቅዱስን ፈርታችሁ ብትወስኑ መልካም ነው።
ቤተክርስቲያንን ለመገንጠል ምናምን ምናምን የሚለው ከቅዱስ ሲኖዶስም ከመንበረ ሰላማም የሚነገረው ንግግር አስቂኝ ነው። ብፁዓን አባቶቼ ቤተክርስቲያን ትገነጠላለች እንዴ? ራሳችሁ ልትገነጣጠሉ ትችላላችሁ እንጂ ቤተክርስቲያን እንኳ ተገንጥላ አታውቅም። በጣም የሚገርመው ወደፊትም ለዘለዓለሙ አትገነጠልም።
አንድ ነገር ግን አለ። ይኽውም አንድ ሰው ወይም ጉባኤ ከቀኖና እና ከዶግማ ውጭ ከወሰነ አለሁ ቢል እንኳ የተገነጠለ መሆኑን መረዳት አለበት።
© በትረማርያም አበባው
አስተያየቶች